2024-06-24 05:12:02
ጣሊያንን ያሸነፍን አማሮች የኦሮሞ ልዩ ኃይል መጣንልህ የሚለን የት ሄደን ነው?????
አጣዬ እዚህ ቦታ ነበረች!
ዳዊት በጋሻው ጥላሁን
ቃሊቲ እስር ቤት
የአጣዬ ከተማ በብልጽግና ትዕዛዝ በወደመችበት ጊዜ ከሙያና ትግል አጋሮቼ መዓዛ መሐመድ ፣ ጎበዜ ሲሳይ ፣ ሙሉጌታ አንበርብር ፣ በላይ ማናዬና ምስጋናው ከፈለኝ ጋር ሆነን ወደ ከተማዋ ስንገባ አጣዬን አጣናት። የሙያና የትግል ብሎም የእስር ቤት ጓዴ ጎበዜ ሲሳይ ከአጣዬ ጉብኝታችን በኋላ "አጣዬ እዚህ ቦታ ነበረች" የሚል አንጀት የሚበላ ዘገባ አሰማን። ሁላችንም እውነትም አጣዬ እዚህ ነበረች ብለን ከንፈር መጠጥን።
ኦነግም ብልጽግናም ያቃጠሏት አጣዬን ካየን በኋላ ሁላችንም የድምጽና የምስል ዘገባ ይዘን ተመለስን። ከአጣዬ ወደ አዲስ አበባ ስንመለስ በመተከልና በወለጋ፣ በአርሲ፣ በሀረርጌ፣ በባሌ፣ በቡኖ በደሌ ተጨፍጭፈን፤ በአዲስአበባም አልቀረልንም። ከተሞቻችንን ማዳንና ማትረፍ፤ ህዝባችንንም መጠበቅ ያልቻልነው ለምን ይሆን ብለን በሰፊው ተወያዬን።
የውይይታችን መቋጫ ግን አከራካሪ አልነበረም።
እኛ አማራዎች ደጃዝማች ፀሐዩ እንቁስላሴ ከ 50 ዓመት በፊት የመከሩንን አለመተግበራችን ነው ብለን ተስማማን
ደጃዝማች ፀሐዩ በወቅቱ የነበረው ሁኔታ ተረድተው እንዲህ ብለው ነበር።
ከእንግዲህ ወዲህ ማንም ቢመጣ ተነሳሁ የሚለው አማራው ሕዝብ ላይ እንጅ ለይቶ የሸዋ፣ የጎንደር፣ የጎጃምና የወሎ አይልም። እኛም ወደድንም ጠላንም፤ የአማራው አንገት አንድ መሆኑን መወቅ አለብን ስለዚህ አማራው መተባበር አለበት ብለው ነበር። ግማሽ ክፍለዘመን ያለፈው ይህ ምክር አሁን የህልውና ትግል ውስጥ ላለነው ሁሉ የሚያገለግል ስንቅ ነው።
ሁሉም ጸረ አማራ ኃይሎች የሚያጠቁን በአማራ ማንነታችን እንጅ በተወለድንበት መንደር አሊያም በያዝነው ሃይማኖት አለመሆኑን ማስታወስ አለብን።
የመጥፋት አደጋ የተጋረጠበት ሕዝብ ተሰባስቦ እንጅ ተበታትኖ ሊድን ከቶ አይቻለውም።
አሁን ብልጽግና በድሮንና በጀት እየደበደበ ያለው ሁሉንም የአማራ ግዛቶች ከመሆኑም በላይ ወደፊት ያቀደውም ከዚህ የከፋ ስለመሆኑ እየነገረን ነው። ዐቢይ አህመድ ከ 10 ቢሊዮን ዶላር በላይ ሀብት አለኝ እዋጋለሁ ብሎ የዛተውን ማስታወስ በቂ ይሆናል።
አንድ አክቲቪስትና የፖለቲካ ሰው ተከበብኩ ሲል፤ አርቲስት ሲሞት...የአማራ እናት ነፍሰ ጡር ሆዷ እየተቀደደ የምትገደለው አማራ ስለሆነች ብቻ ነው። ሌላ ምክንያት የለውም። ከዚህ በላይ ግፍና ስቃይ ከየት ሊመጣ ይችላል ? የምንታገለው ለህልውና ነው ስንል የምራችንን ነው። ከዚህ ለመውጣት ደግሞ መተባበርና አንድ መሆን ግደታችን ነው። በተናጠል በሚደረገው ሩጫ፤ በግል በሚደረግ ጥረት ስር የሰደዱ ጠላቶቻችንን ማሸነፍ አይቻለንም። የግድ አንድ መሆንን ማስቀደም አለብን። እንደ ግለሰብ የምንከበረው እንደሕዝብ ስንከበርና አንድነታችን የጸና ሲሆን ነው። ሕዝባችን በአንድነት ሲከበር ያኔ ሁሉም በግሉ ቀና ብሎ ይሄዳል። በዚህ ወቅት እርስ በእርስ መገፋፋትና መናናቅ ብሎም መሰዳደብ እኛን ከማስገመቱም በላይ እውን የአባቶቻችን ልጆች ነን ያስብላል።
ደራሲና የውጭ ግንኙነት ባለሙያ ሀዲስ አለማየሁ በጣሊያን ጦርነት ወቅት ሰዎች ጣሊያንን መዋጋት ትተው እርስ በእርስ ሲጣሉና ሲቆራቆሱ ቢመለከቱ" ውሾች ሌት ጅብ ሲመጣባቸው እሱን ለመቃወም ይተባበራሉ ፤ ታዲያ ከውሾች የሚሻሉት ሰዎች የጋራ ጠላታቸው ሁሉንም እያጠቃቸው ሲመጣ እያዩ ተባብረው ያንን የጋራ ጠላታቸውን በመቃወም ፋንታ እንደት እርስ በእርሳቸው ለመፋጀት ይነሳሉ? ሲሉ ጠይቀው ነበር። እኔም ይህንን ጥያቄ ደግሜ አነሳለሁ።
እዚህም እዚያም አለመግባባቶችና ጭቅጭቆች እንዳሉ እሰማለሁ። አለመግባባቶች መኖራቸው በራሱ ችግር ላይኖረው ይችላል ነገር ግን በህዝባችን ላይ የዘር ማጥፋት ወንጀል ተፈጽሞበትና ደጃፉ ላይ ድሮንና ጀት እየተተኮሰበት እያየንና እየሰማን እርስ በእርስ መዘላለፍና እልህ መጋባት ተገቢ ካለመሆኑም በላይ የህሊናም የታሪክም ተጠያቂ ያደርገናል።
አሁን በግልጽ ቋንቋ በጋራና በአንድነት መታገልና የሕዝብ ጫንቃ ላይ የተለጠፈውን የፋሽስት ቀንበር ማንሳት ከዚህ ትውልድ ይጠበቃል። የአንድነትና የህብረትን ጠቀሜታ ለእናንተ ማስረዳት ለእናቷ ምጥ እንዳስተማረችው ልጅ መሆን ነው፤ ነገር ግን ለማስታወስ ያህል ይህንን ጹሑፍ ከእስር ቤት ልኬያለሁ።
የአማራ ህዝብ አገርንና መንግስታትን ያሻገረ የሚታይና የሚጨበጥ ስልጣኔ ያለው ከፈጣሪው ትዕዛዝ የማይወጣ ጨዋ ስብዕና ያለው ሆኖ ሳለ በጅምላ እንደ ወንጀለኛ መታየት ከጀመረ ግማሽ ክ/ዘመን ተቆጥሯል።
የአማራ ሕዝብ በማንኛውም መለኪ የተሻለ ሆኖ ሳለ ለዚህ ሁሉ መከራና ግፍ የተዳረው ባለመደራጀቱ፤ አንድ ባለመሆኑና ባለመመካከሩ ነው።
ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ ያልተደራጀ ተፈጀ እንዳሉት ባለመደራጀታችን ጸረ አማራዎች ፈጅተውናል፤ ጨፍጭፈውናል። ተጨማሪ ፍጅቶችንም ደግሰው እየመጣንላችሁ ነው ብለው በሬንጀር እያስፈራሩ ነው።
ጣሊያንን ያሸነፍን አማሮች፤ የኦሮሞ ልዩ ኃይል የሚፎክርብን ለምንድነው የሚለው በሁላችንም አዕምሮ ውስጥ ሊመላለስ ይገባል።
በመላው አለም የምትገኙ ውድ የአማራ ልጆች እናንተ ለህዝባችሁ ስትሉ በብርድም በጸሀይም የምትችሉትን ሁሉ አድርጋችኋል ፤ እያደረጋችሁም ነው። ትግላችን ዓለም አቀፋዊ ተቀባይነት እንዲኖረው የቤተሰባችሁን ጊዜ ቀምታችሁ ሰርታችኋል፤ የተጠየቃችሁትን ሁሉ አድርጋችኋል፤ በዚህ ድርጊታችሁ ሁሉም አማራ ይኮራባችኋል። እኛ እስር ቤት ያለነው ሰዎች ሁሌም እንኮራባችኋለን።
ትግሉ የሚጠይቀውን ሁሉ እያደረጋችሁ ነውና ለዚህ ያለኝን ታላቅ አክብሮት ስገልጽላችሁ ኩራት ይሰማኛል።
በመጨረሻም ውድ ወንድም እህቶቼ የቱንም ያህል ብንሰራ አንድ ላይ ካልቋጠርነው በጎ አይደለም። ስትተባበሩና በህብረት ስትቆሙ በባሌም፤ በጉለሌም፤ በሞያሌም ፤ በሱማሌም ያለው አማራ ቀና ብሎ ይሄዳል። እናንተ ውድ ወንድም እህቶቻችን አንድ ከሆናችሁ የማሸነፍና የመደራደር አቅማችን (Wining and bargaining capacity ) በእጅጉ ይጨምራል።
በሃሳብ ብንለያይም የአማራ አንገቱ አንድ ነውና በአንድነት እንቁም።
ደጃዝማች ጸሀዩ እንቁስላሴና ደራሲና ዲፕሎማት ሀዲስ አለማየሁ እንዳሉት እንተባበር በጋራ እንቁም። በመካከላቸው ምስራቅ ፣ በአሜሪካ ፣ በአውሮፓ ፣ በአፍሪካና በካረቢያን ብሎም በሩቅ ምስራቅ ያሉ ሁሉም የአማራ ልጆች በህብረት ቢቆሙ ይህ አገዛዝ ሁለት ቀን የሚያድር ይመስላችኋል ? በፍጹም ።
እናም በርቱልኝ፤ አንድ ሁኑ ተዋደዱ፤ ተመካከሩ።
ድል ለአማራ ህዝብ
እርግጠኛ ነኝ ከነጻነት በኋላ እንገናኛለን ።
እወዳችኋለሁ
11.7K viewsአባ ስበር, 02:12